Wednesday, August 14, 2013

ጉራ ችርቸራ ትሪዲንግ


እኔ እምልሽ… ባለፈው ወክ እያደረግን… የሆነ ጎረምሳ አይተሸ… "ወይኔ ዳኒዬ! አየኸው ያን ልጅ? ዳኒ ይባላል… አብረን ነው የተማርነው… ፐ! አለባበሱ… አረማመዱ… አወራሩ… በቃ ሁሉ ነገር የሚያምርበት ልጅ… በዛ ላይ ኩራቱ… ጉራውስ ብትል… በነገራችን ላይ፣ ጉረኛ ሰው በጣም ነው የምወደው…" ብለሽ የጎረርሽው… ጉራ የማልችል መስሎሽ እዳይሆንና እዳልጎርር…

ጉራ አሪፍነት መስሎሽ ከሆነ ተሸውደሻል… ጉረኛ ሰው የለየለት ቀጣፊ መሆኑን… ያልተፈጠረን የሚፈጥር፣ ያልሆነውን የሚሆን መሆኑን ካላወቀሽ… በቃ... ተሸውደሻል…

አንድ ነገር ልንገርሽ? አላዋጣ ብሎኝ ትቼው ነው እንጂ… በዚ ምድር ላይ… እንዲሁም በዛኛው… እንደኔ አይነት ቀጣፊና ጉረኛ ሰው አልነበረም… ደግሞ ይሄን ንግግር ጉራ እንዳታደርጊው…

"የተውኩትን ነገር ተመክሬ፣ ተነግሬ፣ ባገር…" አለች ዘፋኟ… በነገራችን ላይ ጨዋታን ጨዋታ ያመጣዋል የለ… ይሄን ግጥም ለጂጂ የሰጠኋት እኔ ነኝ? "እንዴት?" አትይም… ቀኑን በውል አላስታውሰውም… ያኔ ጉራ ስቸረችር ነው… ከተወሰኑ አርቲስቶች ጋር ሰብሰብ ብዬ (ይቅርታ ከበውኝ) እየተጨዋወትኩ… አንዱ አርቲስት… "አንተ በቃ ያለሹፌር አትንቀሳቀስም ማለት ነው? መኪና መንዳት እንዲህ ያስጠላህ?" ብሎ ሲጠይቀኝ "የተውኩትን ነገር…" ብዬ በዜማ ከመመለሴ… ጂጂ ቀለብ አድርጋ… "በናትህ ያሁኑን አባባል ከነዜማው ልዝፈነው ብላ እግሬ ላይ አትወድቅ መሰለሽ…" በቃ… ምና ላርግ… እንደዛ እግሬ ላይ ወድቃ ስትለምነኝ አሳዘነችኝ… በቃ ዝፈኚው አልኳት… ይኸው ታወቀችበት…

እናም… ወደ ጨዋታዬ ልመለስና… በቃ… ላንቺ ስል ጉረኛ ልሆን ነው… ለዛውም አንቱ የተባለ… እንደውም ድርጅት ከፍቼ… ጉራ ችርቸራ ትሪዲንግ የሚባል… በቃ… ከኔ አልፎ እንዳንቺ ጉራን ለሚፈልጉ እንስቶች… በብዛትና በጥራት፣ በጅምላና በችርቻሮ… በተመጣጣኝ ዋጋ አከፋፍላለው… በቃ… የጉራን ዋጋ ሰብሬ ገብቼ ቻይናን ሁላ ጉድ እሰራታለው… አገሩን በሙሉ ጉራ በጉራ አደርገዋለው… አጥለቀልቀዋለው… ከተማው ሁላ የኔን ጉራ ለብሶና ታጥቆ ሲዞር ታይዋለሽ… "ጉረኛ!" ነው ያልሽው? ጉራ አይደለም… አደርገዋለው!

በይ ወደ ገራዬ… ጊዜ የለኝም… የስድስቱ ፋብሪካዎቼን አጠቃላይ ሪፖርት ልሰማ ልሄድ ነው…

ስብሰባዬ ቃሊቲ ስለሆነ በፎር ዊል ድራይቬ ነው የምሄደው… "ኤጭ… ምን አይነት መንገድ ነው… ገና ከመስቀል ፍላወር መንገድ ሳልወጣ ሰዓቱ ሄደብኝ… ምን እንደሚያናድደኝ ታውቂያለሽ? 1ብር ለመልቀም ምድረ ታክሲ የኛን ሰዓት የሚሻማው ነገር… ደሞ በኛ አስፓልት… ነግሬሻለው? የመስቀል ፍላወር መንገድ የፋዘር እንደነበር? ምን ዋጋ አለው… መንግስት ወረሰብን… ልጅ እያለሁ ሳይክል የለመድኩት ሁላ እዚሁ መስመር ላይ ነው… ፋዘር መስመሩን ያዘጋውና ቀኑን ሙሉ ስነዳ እውላለው…"

ለነገሩ አሁንም ቢሆን መስመሩን ለማስመለስ በግሌ ፍርድ ቤት እየተከራከርኩ ነው… ያው እንደምታውቂው የዛሬ ዳኛ በትንሽ ሺ ብሮች ተደላይ ነው… ስለዚህ... የተወሰነች ብር በA3 ካኪ ፖስታ አሽጌ እሸጉጥላቸውና የቤተሰቦቼን ንብረት አስመልሳለው… ካልሆነም ከቤቴ እስከ ቃሊቲ የራሴን መንገድ አሰራና ታክሲ ዘጋብኝ አልዘጋብኝ ሳልል ቀብረር ብዬ እጓዛለው… የማሰራው መንገድ እራሱ ቀለበት መንገድ ነው… ይሄን ምድረ ታክሲና ቪትዝ ከላይ ሆኜ እንደ ቁጫጭ እያየሁ ለመሄድ… ቢበዛ መንግስት በአመት አንዴ የአፍሪካ ህብረት ተሰብሳቢዎችን እናጓጉዝበት ቢለኝ ነው… ያው በአመት አንዴ ብቸገር ነው…

በነገራችን ላይ… ከፈለግሽ… ከናንተ ቤት እስከ ዩኒቨርስቲው ያለውን መንገድም በግሌ አሰራልሻለው… ለዛውም በባለደረጃ አንዱ ተቋራጭ ድርጅቴ… ከታክሲ ጋር ምን አጋፋሽ… እነዛ ምስኪን ቤተሰቦችሽስ በስተርጅና ምን አጎሳቆላቸው… እነዛ አቃጣሪ ጓደኞሽም ቢሆን ማንነቴን ይወቀቱ… መቼም ይህን ለማድረግ በማሰቤ "ጉረኛ!" እንደማትይኝ ነው?

አንድ… እንድታውቂልኝ የምፈልገው ነገር ምን እንደሆነ ታውቂያለሽ? ይሄን ሁሉ ነገር የማደርገው ገንዘብ ተርፎኝ አይደለም… ለጉራም አይደለም… ስልጣኔን ለማሳየትም አይደለም… ጓደኞችሽ እንዲወዱኝ ብዬም አይደለም… ቤተሰቦችሽ እንዲያከብሩኝም አይደለም… አንቺ እንድትወጂኝም አይደለም… ለሌላ ለምንም አይደለም… ያው… ስለምወድሽ ነው፡፡






1 comment: