Sunday, August 25, 2013

10/90… 20/80… 40/60 እና 50


`ህዝቡ መንግስት ከንግድ ባንክ ጋር በመሆን አጭበርብሮኛል ሲል አስታወቀ… ለዝርዝሩ… ገንዘቤ ሽብሩ…

አመሰግናለው ባልደረባዬ… እንደሚታወቀው… መንግስት ባሁኑ ሰዓት… በነዋሪው ቅድመ-ቁጠባ የሚገነቡ የኮንኮሚኒየም ቤቶችን ለመዝራት ማቀዱንና የአፈር ምርመራ… የአረሳ… የጉልጎላና (ነዋሪውን ከየቤቱ)… የምርጥ ሳይት መረጣ ቅድመ ሥራው ከወዲሁ በሚገባ መጠናቀቁን አስታውቋል…

መንግስትን… "ይህን ፕሮግራም እንዴት አሰብከው ጃል?" ብዬ ላቀረብኩለት ጥያቄ እንዲህ ሲል ምላሹን ሰጥቶኛል…

"እንደምታውቁት የመንግስት ዋነኛ አላማ ህብረተሰቡን ማስከፋት ነው… ህብረተሰቡ ሲከፋ ደግሞ ችግሩን ይገልጣል… ችግሩን ሲገልጥ ደግሞ እኛ መፍትሄ ይዘን ብቅ እንላለን ማለት ነው…"
እንዴ?! መንግስት የህዝቡን ጥያቄ የሚረዳው ህዝቡን በማስከፋት ነው ወይስ በሰለጠኑ ባለሙያዎቹ የህዝቡ ፍላጎት ምን እንደሆነ አስጠንቶ ነው?

"ምን አይነት ጥያቄ ነው? እናንተ ጋዜጠኞች ስትባሉ ደግሞ ጥያቄ አመራረጥ አትችሉበትም… ቆይ የህዝቡን በሽታና መከፋት ካላወቅን… አመመኝ… ደከመኝ… እንዲህ ሆንኩ… እንዲያ ሆንኩ… እዚህ ጋር ቆረጠኝ… እዛጋ ፈለጠኝ ካላለን… መንግስት ጠንቋይ ነው እንዴ በግምት አስጠንቶ የሚደርስበት? ለጥናትና ለምርምር ብለንስ ምን ትርፍ ወጪ አስወጣን… ህዝቡ… እራሱ… ሲበላው ይናገር የለም እንዴ… እኛ ማን ነንና ነው ህዝቡ ሳይበላው የምናክለት…"

ታዲያ… እንደዛ ከሆነ… በቤት ጉዳይ… የህዝቡን መከፋት እንዴት ደረሳችሁበት…

"ያው እሱማ… መንግስት አይኑም ጆሮውም ሰፊ ነው… ብዙ ነው… ሲባል ሰምተህ የለ… ታዲያ ይሄ ጆሯችን ምን ሰማ መሰለህ… ህዝቡ አዲስ አመት በመጣ ቁጥር የሚያቀነቅናትን የአዲስ አመት ግጥም…"

ምን የሚለውን?

"‘እንኳን ቤትና የለኝም አጥር እደጅ አድራለው ኮከብ ስቆጥር' የሚለውን ነዋ… በየአመቱ የቤት ባለቤት ብናረገውም… ይቺ ግጥሙ ይኸው እስከዛሬ ድረስ አልተለወጠችም… ታዲያ ለዚህ መፍትሄ የሚሆነው… ለህዝቡ በሰፊው… ፕሮጀክት ቀርፆ… ቤት መዝራት እንደሆነ ደረስንበትና ከንግድ ባንክ ጋር ሆነን አረሳችንን ጀመርን…"

ይህ በእንዲህ እንዳለ… በተመሳሳይ ዜና… መንግስት ይህን የቤት ልማት ፕሮጀክት አብረን በደቦ እንዝራ ብሎ ንግድ ባንክን ሽማግሌ የላከበት መሆኑ የተገለፀ ሲሆን… ንግድ ባንክም በበኩሉ… ለጋራ ጥቅማችን እስከሆነ ድረስ ምን ገዶኝ በማለት አጉራአጠናኛ ማለቱን ሰምተናል…

በመሆኑም… ንግድ ባንክ በወራት ከፋፍሎ… የብር ለቀማ ስራውን ካከናወነ በኋላ… 10/90… 20/80… እንዲሁም 40/60 ቤቶችን ከመንግስት ጋር ሆነን አብረን እንዘራላችኋለን ካለ በኋላ… ብዙም ሳይቆይ… የህዝቡን ዘፈን መልሶ ለራሱ እንዲሉ… ንግድ ባንክም እንዲህ ሲል ተደምጧል…

እኔም እኮ… ለወጉ እንጂ… ነፍስ ያለው ቤት የለኝም… ይኸው ከተመሰረትኩ ጀምሮ ዝንት አመት ሙሉ የማስበው… የማሰላስለው ይሄንኑ ነበር… እኔም እንደ ህዝቡ ስለ ቤት ስዘፍን ከርሜያለው… በመሆኑም… እድሜ ለዚህ ምስኪን ህዝብ (ብር አምጣ ሲሉት እሺ ነው… በዚህ ውጣ ሲሉት እሺ ነው… በዛ ተነቀል ሲሉት እሺ ነው…) እንዲሁም እድሜ ለቤቶች ልማት ፕሮጀክት… አሁንማ ካዝናዬ ሞልቶ ብዬ… በአገር ውስጥና በውጭ አገር ተቋራጭ ድርጅቶች አስጠንቼ… የቅርንጫፎቼ ሁሉ ዋና የሆነውን አውራ ብር መሰብሰቢያ ቤቴን… ባለ ሃምሳ ፎቅ ልሰራ ነው… እ-ን-ቁ-ጣ-ጣ-ሽ ማለት እንዲህ ነው… እልል በሉልኝ… ሲል በአፉ ሙሉ ተናግሯል… በካዝናው ሙሉም ብር ይዟል…

ጉድ ሳይሰማ መስከረም አይጠባ ማለት ይሄኔ ነው… ከኋላ የመጣ አሉ… መንግስት እንኳን ይሄን ሁሉ አመት በአንድ ቤት እየኖረ… ለራሴ ቤት አማረኝ ሳይል… ለህዝቡ ምሬት በአንድ ቤት እንደቆመ… ይኸው አጅሬ ንግድ ባንክ ከኋላ መጥቶ… ለምን ህዝቡ ብቻ ኮከብ ይቆጥራል… እኔስ ለምን ለኮከብ አልቀርብም ብሎ ባለ 50 ፎቅ ቤት ሊያሰራላችሁ ነው…

ለነገሩ ንግድ ባንክ እውነቱን ነው… ብር ካገኙ አይቀር እንዲህ ነው… መቼም ማናችንም ጥሩ ፈራንካ ብትኖረን መሬት ላይ አንድበሰበስም… ባለ አንድም ትሁን፣ ባለሁለት… እንጣዋን ሰርቶ… ከሰው በላይ ከፍ ማለት ነው እንጂ… የምን ከጭቃና ከደሃ መጋፋት ነው… ፈረንጆቹ ብር ስላላቸውም አይደል መሬት ደበረችን ብለው ወደ ጠፈር ከፍ እንበል ያሉት…

ለማንኛውም… ንግድ ባንክን… እሰየው… ጎሽ… ደግ አደረክ… አንተም ባለ 50 ፎቅህን ስራና እኛም ባለ አስራ ሁለቷ ላይ ሆነን ጭቃንና ድህነትን አብረን እንጠየፋለን በሉልኝ፤ ከዛም… ከመሬቷ ከፍ ብለን… ኢትዮጲያ ለዘላለም ትኑር! እንንላለና…
  



No comments:

Post a Comment