Sunday, August 25, 2013

ህፃንኛ-2


ሁለት በ ሁለት ፍቅር

ተወልጄ ያደኩት ከእናቴ ጋር ነው… እናቴም የምትኖረው ከኔና ከእናትና-ልጅ(አረቄ) ጋር ነው… በ ሁለት በ ሁለት ቤታችን ውስጥ…

ታዲያ… ፍቅር የሚገለፀው ሁሌም በሁለትዮሽ ብቻ ይመስለኛል… ለምሳሌ እኔና እናቴ… ሁለት ብቻ ነን… የአረቄ ጠርሙሱ ላይ ያሉት እንስሶች… አጋዘን መሰሉኝ… እናትና ልጅ ይሏቸዋል… እነሱም ሁለት ናቸው… እኛ ግድግዳ ላይ የተሰቀለው የእመቤታችንና የልጇ ምስል… እነሱም ሁለት ናቸው… ከሩቅ ደግሞ… የነዚህን ሁለት ነገሮች ፍቅር ከላይ ሆነው የሚጠብቁ... ሁለት መልዓክት አሉ… ልክ የእመቤቴና የልጇ ምስል ላይ እንዳሉት…  

የሰፈር ልጆች… "አባትህ የት ነው? አባት የለህም እንዴ?" እያሉ ይጠይቁኝና ሊያበሽቁኝ ይሞክራሉ… እኔ ግን አልበሽቅላቸውም… እንደውም እንደኔና እማዬ ሁለት ባለመሆናቸው አዝን ነበር… ምክንያቱም ሁሉም ጎረቤቶቻችን ሲጨቃጨቁ… ሲጣሉ… ሲደባደቡ አያለው… እናም እንደኔና እማዬ ሁለት ባለመሆናቸው ነው ብዬ አስባለው… እኔና እማዬ አንድም ቀን ተጣልተን አናውቅም… ሁለት በ ሁለት ቤታችን ውስጥ ሁልጊዜም ደስ የሚል ፍቅር አለ… ጥልና ፀብ እራሱ ምን እንደሆነ ያወኩት በጎረቤቶቻችን ምክንያት ነው…

አንዳንድ ጊዜ ቤታችን ከሁለት በ ሁለት ትንሽ ብትሰፋ እኔና እማዬ እራሱ ዝም ብለን የምንጣላ ይመስለኛል… ምንም እንኳን ሁለት ሰው ባይጣላም…

አባት ግን ምን ይሰራል? አባት ኖሮኝ ባያውቅም… የሌሎች ልጆች አባቶች ሁሌም ሲቆጧቸውና ሲገርፏቸው… ልጆቹም አባቶቻቸውን ሲፈሩ ነው የማውቀው… አባቶች ልጆችን ብቻ አይደለም የሚቆጡትና የሚገርፉት እናቶችንም ጭምር ነው… አንዳንድ ጊዜ ሳስበው… ግድ ሆኖባቸው እንጂ… እንደኔና እማዬ እደለኛ ሳይሆኑ ቀርተው እንጂ… የጎረቤት ልጆችና እናቶች እራሱ አባት ባይኖራቸው የሚመርጡ ይመሰልኛል…

አባቶችም ለክፋትና ለፀብ ብቻ የተፈጠሩ ይመሰልኛል… ለዛም ነው… ጦር ሜዳ የሚልኳቸው… ለምሳሌ እኛ አረቄ ቤት የሚመጡት ሁሉም አባቶች ናቸው… ታዲያ… ሰክረው ጮክ ብለው ከማውራትና ከመሰዳደብ ውጪ ሌላ ስራ የላቸውም… ታዲያ አባት ምን ይሰራል? የእመቤቴ ማሪያምና የልጇ ምስል ላይ እራሱ አባት የለም… ስለዚህ ፍቅር የሚገለፀው በሁለት ነው ብዬ አስባለው…

ሰው ከሁለት በላይ ከሆነ ሁሌም የሚጨቃጨቅ ይመስለኛል... ለምሳሌ የኛ ቤት… ሁለት በ ሁለቷ… አረቄ ጠጪዎች ሲመጡባት… ወዲያው ቀውጢ ትሆናለች… እኔና እማዬ ለሁለት የዘራንባት ፍቅር ወዲያው በጭቅጭቅና በፀብ ይደፈርሳል…

እናም… በቃ… ሰው ከሁለት በላይ ሆኖ መኖር የለበትም ብዬ አስባለው… ለዚህም ይመስለኛል የሰውነት ክፍሎቻችን እራሳቸው በአብዛኛው ሁለት ሁለት ሆነው የተፈጠሩት… ሁለት እጅ… ሁለት እግር… ሁለት ጆሮ… ሁለት አይን… እንዲሁም… እንደ ነገረኛ ጎረቤታችን… ሁለት ምላስ…



No comments:

Post a Comment