Monday, July 22, 2013

ለምን?

ቦሌ መስመር ላይ ነኝ… ጃፓን ኢምባሲ አካባቢ… ወደ ድልድይ የሚሄድ ታክሲ እየጠበቅኩ… እኔ በቆምኩበት ፊት ለፊት (ተሻግሮ) ባለው አስፓልት የታክሲ ግፊ ላይ ቀልቤ አረፈ…

ሰዉ አስፓልት ላይ ሳይሆን የእግር ኳስ ሜዳ ላይ ያለ ነው የሚመስለው… ፋወል በየአይነቱ ነው… በሰዉ የግፊያና የብሎክ ስትራቲጄዎች ተደምሜ አይኔን ሳልነቅል ቀረሁ… ታደያ ይሄኔ… ድንገት… አይኔ አንዲት እንስት ላይ አረፈ… "ዊንታ!" እንዴ! "ዊ-ን-ታ! እኔ አላምንም!"…

ዊንታ… ድሮ የኤለመንታሪ ተማሪ እያለው የምወዳት ልጅ ነበረች… ከኤለመንተሪ ከወጣሁ ጀምሮ አግኝቻትም፣ አይቻትም አላውቅም… ያ የልጅነት ውበቷ ላይ አሁን ደግሞ ዝነጣና እራስን መጠበቁ ተጨምሮበት ቀውጢ ቺክ ሆናለች…

ወዲያውኑ ተሻግሬ ላናግራት ወሰንኩ… እናም መኪና አይቼ ልሻገር ስል የመሃል አካፋይ መስመሩ በአፈር መሞላቱን አስተዋልኩ… አይኔ በሚችለው ርቀት ወደ ላይም ወደ ታችም ባይ ዜብራ መስመር የሚባል ከየት ይምጣ… ምንም እንኳን መንገድ ስሻገር በአብዛኛውና በተቻለኝ አቅም ዜብራ ፈልጌ ቢሆንም አሁን ግን የፕሪንሲፕል ሰዓት አይደለም… በቃ በአፈሩ ላይ ለመውጣትና ለመሻገር ወሰንኩኝ… ነገር ግን የመንገድ አካፋይ ቦታው የጉልበቴን ቁመት በሚያህል ኮንክሪት ዳርና ዳሩ ታጥሯል… በዛ ላይ ዝናብ ጥሎ ስለነበር አፈሩ ጭቃ ሆኗል… አማራጭ አልነበረኝም ዝም ብዬ ወደ ላይ መውጣት ጀመርኩ ዜብራ መስመር ፍለጋ…

ዊንታን አሁንም እያየኋት ነው… እሷ አላየችኝም… ስልኳን እየጎረጎረች ነው… ታክሲ መጣ… ስልኳን ትታ ግፊያውን ተቀላቀለች… ጮኬ መጣራትም አማረኝ… ወዲያው ኸረ... ይ-ደ-ብ-ራ-ል ብዬ ተውኩት… ታክሲው ከለለኝ… ወይኔ! ገባች? ሺት! አትታየኝም… ኦልሞስት መሮጥ ጀመርኩ…

ዜብራ ላይን አየሁ… ትንሽ ነው የቀረኝ ልደርስ ነው…. ታክሲው ተንቀሳቀሰ… ቆምኩ… የስ!… የስ! አለች… እድል አልቀናትም…
ምን ሆኜ ነው ግን? ለምንድነው ይሄን ያህል ላናግራት የፈለኩት? ማን ያውቃል… እግዜር ምን አስቦልኝ እንደሆነ… ለምንስ ታክሲው ውስጥ አልገባችም? በግፊያው ተሸንፋ የሚለውን ማሰብ አልፈለኩም… በቃ እግዜር እንደ አዳም በቀላሉ ሄዋኔን ከጎኔ ሻጥ ሊያደርጋት አስቦ ይሆናል አልኩ…

ተሻገርኩ… አሁን ደግሞ ወደሷ እየወረድኩ ነው… እንደገና ወደ ታች… ሌላ ታክሲ… ሺት! ልጣራ ይሆን… "ዊ.." ወዲያው ተውኩት… ሺት! ኡፍፍፍ… አጎነበስኩ… ትንፋሽ ቁርጥ ቁርጥ እያለ ነው… ሺት! ዊንታ ታክሲው ውስጥ ገባች…

ቆምኩ… የወቀሳ፣ የስድብ፣ የማማረር ሰዓት… አንደኛ- የኢትዮጲያ መንገዶች (ኮሮኮንቾች) ባለስልጣን… ሁለተኛ- ቻይና…

ሶስተኛ-ታክሲ… አራተኛ- ወያላ… አምስተኛ-ዝናብ… ስድስተኛ- ጭቃ… ሁሉንም ለመፃፍ የሚከብድ ፀያፍ ስድቦችን ተሳደብኩ…

እግዜርስ ቢሆን… መጀመሪያ ለምን አሳየኝ … ለምንስ በመጀመሪያው ታክሲ እንድትሄድ አላደረጋትም… ለምን ተስፋ ሰጠኝ…

እኔስ ብሆን… ለምን አልተጣራሁም… ለምንስ በደንብ አልተራመድኩም… ለምንስ አልሮጥኩም…

እሷስ ብትሆን… ለምን ከፊቴ ቆመች… ለምን አላየችኝም… ለምን ስልኳን ትጎረጉራለች… ለምን ተጋፍታ ገባች…
ለምን… ለምን… ለምን…

No comments:

Post a Comment