Monday, July 22, 2013

ከተቀማጭ ወደ ሯጭ ፕሬዝዳንት

የሆነ ሰሞን ከተማችን ላይ ኢንፎቴይመንት የምትል የፅሁፍ ውጤት ነበረች… በነገራችን ላይ ‘ኢንፎቴይመንት’ኢንፎርሜሽንን እና ኢንተርቴይመንትን በማዋሃድ የተፈጠረች ቃል ነች... እኔ ደግሞ ዛሬ የማጫውታችሁ ፖሊቴይመንት የምትባል ወግ ነው ፖለቲካን ከኢንተርቴይመንት አዋህጄ…

ዘንድሮ መቼም ጦቢያችን አልተቻለችም፣ በድል ላይ ድል፣ በሪከርድ ላይ ሪከርድ… አዳዲስ አስፓልቶች፣ አዳዲስ ካቢኔ፣ አዲስ ጠቅላይ ሚኒስቴር… የአባይ ግድብ፣ የከተማ ባቡር… ሌላም፣ ሌላም…

አዲስ አበባማ አይናችን እያየ እንደ ስሟ አበባ ልትሆን ነው… ከጥቂት አመታት በኋላ ደግም አገራችን አራሷ የማናውቃት ኢትዬጲያ ልትሆንብን ነው…

በተለይ በዚህ አመት ልክ እንደ ዋልያዎቹ ማልያ፣ ‘ኢትዮጲያዊነቴ ኩራቴ’ የሚለው ቲ-ሸርት እንደ ጉድ እየተቸበቸበ ይመስለኛል…

ለምሳሌ… ይሄ የሰሞኑ የካቤኔ ሹም ሽረት… ሲቪሪ ሜሞሪ ሎስ ቢያጋጥመኝ እንኳን ስማቸውን የማልረሳውን የሚኒስቴሮች ስም ከዋናው መድረክ በስተጀርባ ያደረገበት ሁኔታ ነው ያለው… እውነቴን እኮ ነው! ለውጥም በሉት ልወጣ... የስንት ሚኒስቴሮችን ስም እንደ አዲስ እንደምንሸመድድ አስባችሁታል?

ድሮ፣ ድሮ "እገሌ የሚባል ሚኒስቴር መ/ቤት የት እንደሆነ ታውቃለህ?" ብሎ ሰው ሲጠይቀኝ ከሚኒስቴር መ/ቤቱ ስም ይልቅ የሚኒስቴሩ እና የሚኒስቴር ድኤታው ስም ነበር ቶሎ ወደ አይምሮይ ከች የሚለው… የሚኒስቴር ስምና የሚኒስቴር መስሪያ ቤት ስም ልክ እንደ አረፍተነገር የማይለያዩ ነገር ይመስሉኝ ነበር… ልክ "አበበ…" ሲባል "…በሶ በላ" የሚለው እንደሚመጣብኝ አይነት…

ይሄ… አዲስ ነገር በመፅሄት እንጂ በህይወቱ የናፈቀው ህዝብ በአሁኑ ሰዓት አዲስ፣ አዲስ ኢትዬጲያ እየሸተተችው ያለበት ሁኔታ ነው ያለው.. አስቡት እስቲ እቺን ጋዜጣ እንኳን ሳይቀር በባቡር ላይ ሆናችሁ የምታነቡበት ጊዜ እኮ እውን ሊሆን ነው…

መቼም… ያልሰማህ ስማ፣ የሰማህ አሰማ ነውና ብሂሉ… ከተማው ላይ የሚናፈሰውን አዲስ ወሬ ሰምታችኋል? ሰምታችሁ ካልሆነ… ቀጣዩ የኢትዮጲያ ፕሬዝዳንት የመሆን እጣ ፋንታ ሊደርሳቸው ከሚችሉ ግለሰቦች መካከል አንዱ… እውቁ፣ አትሌት ሀይሌ ገብረስላሴ መሆኑን በሰፊው እየተናፈሰ ነው…

ይህ ወሬ አሉባልታ ከመሆን አልፎ እውነት-ባልታ ከሆነ ለሀይሌም ይሁን ለአገራችን ትልቅ ስኬት ነው፤ እኛም ልክ እንደ አማሪካ ‘የስ ዊ ካን’ ወይም እንደ ሀይሌ ‘ይቻላል!’ የምንልበት ጊዜ ሊመጣ ነው ማለት ነው…

‘ዌል እንግዲክ’ እንደዛ ሊሆን ነው ብለን እናስብና… ምን አይነት ለውጦች ሊኖሩ ይችላሉ ወደሚለው እንሂድ…

እስከማስታውሰው ድረስ… ኢትዬጲያ ፓርሊያመንታሪ ስርዓት ተከታይ ከሆነችበት ጊዜ ጀምሮ የኢትዬጲያ ፕሬዘዳንት ስራ ምንድነው ብላችሁ ብትጠይቁኝ… አንደኛ- አሪፍ ወንበር ላይ ቁጭ ብሎ ለአዲስ አመት እንዲሁም ለህዝባዊና ሀይማኖታዊ በዓላት የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት ማንበብ፤ ሲቀጥል፣ የምረቃና የሽልማት ፕሮግራሞች ላይ መሳትፍ ነው… እነዚህም ዝግጅቶች ላይ አጭር ንግግር አድርጎና ባስ ካለም ሪቫን ቆርጦ ቁጭ ማለት ነው… ባጭሩ በፓርላመንተሪያን አገራት ያለው የፕሬዝዳንት የስራ ሃላፊነት የአገር ተጠሪነት እንደመሆኑ ‘ቁጪያ’ እንጂ ያን ያህል ሩጫ አይበዛውም…

እንግዲክ… ሀይሌ ፕሬዝዳንት ሲሆን እንዴት አስችሎት ሊቀመጥ ነው? እስቲ አስቡት… ቤተ-መንግስቱ ውስጥ የመሮጫ ትራክ ሊሰራ ነው ማለት ነው… በቀን ሁለቴ ጠዋትና ማታ ትሬይኒንግ… ስራ ካልተደራረበ ደግሞ በሃይሌ ፅናት ቀኑን ሙሉ ግቢዋን ሊዞራት ነው…
እርግጠኛ ነኝ ሀይሌ የአዲስ አመት የመልካም ምኞት ሲሰጥ እንደ ቀደምት ፕሬዝዳንቶች አሪፍ ወንበር ላይ ቁጭ ብሎ ሳይሆን… ልክ የመሮጫ ትራክ ላይ እንዳለው የሩጫው ‘የመጀመሪያ መስመር’ (start line) አለ አይደል፣ እሱ መስመር ላይ አሮጌው አመት የሚል ይፃፍበታል ከዛ ‘የመጨረሻው መስመር’ (finishing line) ላይ ደግሞ አዲሱ አመት የሚል ይፃፍበትና ‘ፕሬዝዳንት’ ሀይሌ ገብረስላሴ ከመጀመሪያው መስመር ተነስቶ ወደ መጨረሻው መስመር በመሮጥ ሪቫኑን ይበጥሰውና፣ በኩራት… የባንዲራ ዘንግ በአፉ ሳይሆን በእጁ ይዞ… "እንኳን ከአሬጌው አመት ወደ አዲሱ አመት በሩጫ አደረሳችሁ!" ይለናል ማለት ነው…

ሌላው ደግሞ… የሆነ የቦኖ ውሃ ወይም የአዲስ ትምህርት ቤት ምረቃ ላይ ሀይሌ ሪቫን እንዲቆርጥ መቀስ ሲሰጠው ያው እንደለመደው መቀሱን ጥሎ እየሮጠ ሄዶ ሪቫኑን በደረቱ ይበጥሰዋላ… ከዛ ስፖርት-ኮላ አሁን ገበያ ላይ ስለሌለ ኮካ-ኮላ በአንድ ትንፋሹ ይጨልጥና… እምምምም…. "ኢ-ት-ዮ-ጲ-ያ!" ይላል… (ኮካ-ኮላዎች፣ በዚህ አጋጣሚ ለማስታወቂያዋ ሰሞኑን ቢሯችሁ እመጣለው)

በቃ ምንአለፋችሁ… በአጭሩ… ኢንቨስተር፣ ሯጭ፣ አዝናኝ፣ የአገር ሽማግሌ… ሌላም ሌላም… የሆነ ፕሬዝዳንት ሊኖረን ነው… አልቸኮላችሁም? ቀላል ቸኩያለው!
ቆይ ግን ሀይሌ ፕሬዝዳንት ሲሆን ሱፍ ነው ወይስ የብሄራዊ ቡድኑን ቱታ የሚለብሰው? መቼም ሱፍ ከለበሰ አዲዳሶች (adidas Company) የሚቀየሙት ይመስለኛል… ያለበለዚያ ግን አዲዳሶች እራሳቸው ሱፍ ማምረት ሊጀምሩ ነው ማለት ነው… እርግጠኛ ነኝ ደግሞ እንደሚያደርጉት… ምክንያቱም እንኳንስ ፕሬዝዳንት ሆኖ ቀርቶ ድሮም ሀይሌያችን አለም አቀፍ ተፅኖ ፈጣሪ ነዋ!

እኔ እምለው… ሀይሌ ፕሬዝዳንት ሲሆን መሮጥ ያቆማል ማለት ነው? ቢያንስ በአለም አቀፍ ደረጃ እንኳን ባይወዳደር ታለቁ ሩጫ ላይ አይሮጥም? እንደኔ እንደኔ ግን በአለም አቀፍ መድረክ ቢያንስ አንዴ ሮጦ ‘ባለ ወርቅ መዳሊያው ፕሬዝዳንት’ ተብሎ ጊነስ ላይ ስሙን ማስመዝገብ አለበት…

ከዛ ወደ ኢትዬጲያ መጥቶ አቀባበል ሲደረግለት ማሰብ ነው… ክቡር፣ አትሌት፣ ‘ፕሬዘዳንት’ ሀይሌ ገብረስላሴ በምክትል ፕሬዝዳንትና እንትን ሚኒስቴሩ በአቶ እገሌ የአበባ ጉንጉንና ይሄን ያህል ሄክታር መሬት ስጦታ በሽልማት መልክ ተበረከተላቸው ምና ምን አይነት ዜና እንሰማለን… አሁንም… እንደኔ እንደኔ ሀይሌ ቢያንስ የጊነስ ቡኩ ሪከርድ ቀርቶበት ለመሬቷ ሲል ቢሮጥ አሪፍ ነው… ምክንያቱም የመጨረሻው ነዋ የምትሆነው… ኋላ ፕሬዝዳንት ሲኮኑ ሀብት ማስመዝገብ ምና ምን የሚባል ነገር ስላለ ማለቴ ነው…

እርግጠኛ ነኝ ሀይሌ ፕሬዝዳንት ሲሆን የቱሪስቶች ቁጥር እንደሚያሻቅብ… በቃ አገራችን ከታሪካዊ መስህቦቿ ባሻገር አዝናኝ የቱሪስት መስህብ ልትሆን ነው… ከነ ሉሲ ይበልጥ ቤተ መንግስቱ በበርካታ ቱሪስቶች ሊጎበኝ ነው… (Run with the president) ‘ከፕሬዝዳንቱ ጋር ሩጥ’ የሚል ፕሮግራም እያዘጋጁ ይሄን ዶላር መሰብሰብ ነው…

ሌላው ስፖርት ኮሚሽኑን በሚኒስቴርነት ደረጃ እንዲቋቋምም ሎቢ ሊያደርግ ይችላል የሚል ግምት አለኝ… እናም የሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች አመታዊ የበጀት ድልድል ሲወጣ ዳጎስ ያለ ገንዘብ ለስፖርታዊ መሰረተ ልማቶች እንደሚመደብም ከወዲሁ መገመት አያዳግትም… ፓርላማው ባያፀድቀው እንኳን ሀይሌ ከግል አካውንቱ ፈሰስ ሊያደርግ ይችላል የሚል ግምት የለኝም… ምክንያቱም እሱ የቢዝነስ ሰው ነዋ! "ቀጥተኛ ትርፌ ምንድነው?" የሚል ጥያቄ መጠየቁ አይቀርም…

ዌል እንግዲክ… የዛሬውን ፖሊቴይመንቴን በዚሁ ላብቃ፤ ስለ ሀይሌ ፕሬዝዳንትነት ሳስብ የታዩኝ ጉዳዬች ለዛሬ እኒህ ናቸው፤ ሰንበት ብሎ አዳዲስ ሃሳብ ከመጣልኝ፤ እንደገና እመጣባችኋለው… ኢትዮጲያ ለዘላለም ትኑር!
.....................
በነገራችን ይህች ፅሁፍ በቀጣዩ ማክሰኞ በኢትዮ-ምኀዳር ላይ ትወጣለች፤ በዚህ አጋጣሚ ጋዜጣውን ገዝታችሁ ሌሎችንም አሪፍ፣ አሪፍ ፅሁፎች እንድታነቡ እጋብዛችኋለው…

No comments:

Post a Comment