Sunday, May 20, 2012

ወፍ የለም!


ቋንቋ ይፈጠራል፣ ይስፋፋል፣ ይለመዳል!

ቋንቋ ምንድን ነው? ብዬ ስጠይቅ፣ ቋንቋ መግባቢያ ነው የምትል ቅልብጭ ያለች ግና ውስጠ-ወይራ የሆነች መልስ አገኘው፤ እናም እንደገና ጠየኩ፣ አውን ቋንቋ መግባቢያ ብቻ ነው? ስል፤ ምክንያቱም አሁን አሁን የምሰማቸው መጤ ቃላቶችና ሀረጎች የቋንቋን መግባቢያነት ሳይሆን ይልቁኑም ግራ-ማጋቢያነት ማሳያ በመሆናቸው ነው፡፡ እርግጥ ነው ትርጉሟ በደፈናው ቋንቋ ማግባቢያ ነው አለች እንጂ ግራ ይሁን ቀኝ በውል አልጠቀሰችም፤ ለዚህም ይመስላል እንደፈለግነው ግራም ቀኝም የምናንቋቋው/ቋንቋን/፡፡

ቋንቋ ሆሄያት፣ ወደ ቃል፣ ቃላት ወደ ሀረግ፣ ሀረጎች ወደ አረፍተነገር፣ አረፍተነገሮች ወደ አንቀፅ… የሚቀጣጠሉበት ተራ የድምፀት እርባታ ብቻ ሳይሆን የዚያን የተናጋሪውን ማህበረሰብ እሴቶች፣ ባህል፣ ስነምግባራት፣ ትውፊቶች፣ ወዘተ ማሳየት የሚችል እምቅ ሀይል አለው፡፡
በነገራችን ላይ ቋንቋ የስልጣኔን ደረጃም የማሳየት ብቃት አለው ብዬ በግሌ አምናለው እንዴት ማለት መልካም፣ ጉዳዩ ሰፊ ጥናትን ሊጠይቅ የሚችል፣ ምናልባትም ተጠንቶበት ሊሆን የሚችል ነው፤ ቲየሪው የመጣልኝ በስልጣኔ ዙሪያ ከአንድ ጓደኛዬ ጋር በስፋት አያወጋን በነበረበት ወቅት ነው እናም የሚከተለውን ዲስኩር ደሰኮርኩለት፤
"…እኛ ኢትዮጲያዊያን እኮ በብዙ ነገር ግንባር ቀደም ከሚባሉ አገራት ተርታ የምንመደብ ነን ለምሳሌ ብትወስድ የራሳችን ፊደል ያለን ነን፡፡ ዳሩ ምን ዋጋ አለው ፊደላቶቻችን እራሳቸው የአስተሳሰባችንን ሲምፕልነት ያሳያሉ፤ አብዛኞቹ ፊደሎች ቅርፃቸው ቀላል ነው፣ የሁለትና በዛ ቢባል የአራት መስመሮች ውህደት ለምሳሌ ውሰድ - ሀ፣ ተ፣ በ፣ ቸ፣ ፐ… እንደው ትንሽ ለማወሳሰብ ስንሞክር ቀለበት ይጨመርባቸዋል - ዐ፣ ወ፣ ቀ፣ ጨ… በአንፃሩ እነ ቻይና፣ ህንድ፣ እንዲሁም እስራኤልን እንደምሳሌ ውሰድ ፊደላቶቻቸው እንደመንገዶቻቸው እርስ በእርሳቸው የተጠላለፉ ስዕል የሚመስሉ ናቸው፡፡ ይህም የአእምሮ ብቃታቸውን የሚያሳይ አንዳች ነገር ነው ብዬ አስባለው፡፡ ቅም-ቅም አያቶቻችን የዋህና ቀጥተኞች ስለነበሩ ምን ነገር አወሳሰበን ብለው ነው -ሀ- እና -ፐ-ን የፈጠሩት ትለኝ ይሆናል፤ እኔ ግን የሚሰማኝ አእምሯቸው እስከዛ ድረስ ብቻ ማሰቡ ወይም ስንፍናቸው ነው፤ የዋህ እና ቀጥተኛ ቢሆኑ ኖሮማ ቅኔ የሚባል ነገር ባልፈጠሩ፡፡
እውነቴን እኮ ነው እነ ቻይና በአሁኑ ሰዓት በስልጣኔውም በኢኮኖሚውም አሉ ከሚባሉ አገራት ተርታ የሚመደቡ ናቸው፤ ታዲያ ይህ የስልጣኔ ደረጃ እነዚህ አገራት በአጋጣሚ የደረሱበት እኛ ደግሞ የክፉ ዕጣችን ሆኖ ነውን? ወይንስ የአእምሮ እድገትና የአስተሳሰብ ደረጃችን ያመጣው ልዩነት? ይህን ጅምር-ቲየሪ ኮፒ ራይቱ እንደተጠበቀ ሆኖ ሌሎች የዘርፉ ምሁራን ጥልቅ ምርምር /እንደ ቻይናዊያኑ ማለቴ ነው/ ቢያደርጉበት ብዬ አልፌዋለሁ፡፡
እናም ወደ ፅሁፌ መነሻ ስመለስ ቋንቋ ይወለዳል፣ ያድጋል፣ ይሞታል! የምትል መፈክር መሰል ዑደተ-ቋንቋን የምታስረዳ ሀረግ ታወሰችኝ እርግጥ ነው ይህ ዑደት የማይታበይ እውነታን የተላበሰ ቢሆንም የኔ ወግ የሚያተኩረው በቋንቋ ውልደት ላይ ብቻ ይሆናል፡፡ እናም ውልደቱን እራሱ እንዲህ በዑደት አስቀምጬዋለሁ ቋንቋ ይፈጠራል፣ ይስፋፋል፣ ይለመዳል! ስል፡፡
እንደሚታወቀው ቋንቋ የሚዳብረው ወይም የሚያድገው በውስጡ ያሉ ቃላቶች ገላጭነትና ትርጉም ሲሰፋ እንዲሁም የተመሳሳይ ቃላት አማራጮችን ተከትሎ ነው፡፡ ታዲያ አማርኛችንም እንደ አንድ ጠንካራ ቋንቋ ብርቱ ሆኖ ከትውልድ ወደ ትውልድ እንዲሸጋገር እንደ ዘመኑ ለዘመኑ የሚገቡ ዘመን-ወለድ ቃላቶችን እየፈጠረ፣ በነባር ቃላት ጥመረታዎች አዳዲስ ቃላትን እየጨመረ፣ ከሌሎች ቋንቋዎች እንደ ወረዱ እየወረሰ እንዲሁም በሌላም በሌላም መንገዶች እየታገዘ እድገተ-ህልውናውን ማስጠበቅ አለበት፤ survival of the fittest / ሃይል ያለው ርትዕ አለው/ አይደል ጨዋታው፡፡   
የዛሬ ወጌን ለመጠረቅ ያዳዳኝ የሰሞነኛ አዳዲስ ቃላቶች መብዛት እንዲሁም የነባር ቃላት በአዲስ መልክ አዲስ ትርጓሜ ይዞ ብቅ ማለት ነው፡፡ እነዚህ ቃላት ወይም ሀረጎች በአብዛኛው በጥቂት ቀልድ አዋቂ ወጣቶች የሚፈጠሩ ሲሆኑ ቀስ በቀስ ግን እየተስፋፉ ይመጡና ኋላ ላይ ይለመዳሉ እንደ አንድ የቋንቋው አካል ይቆጠራሉ ማለት ነው፡፡ ለምሳሌ መስሚያዬ ድፍን ነው የሚባል አማርኛ መጥቷል፣ እረ እንደውም አንዱ ጓደኛዬ በአጭሩ MD ብሎኛል /መስሚያዬ ድፍን ነው/ መሆኑ ነው፡፡ ይህቺ ሀረግ ወይም አረፍተነገር በአሁኑ ሰዓት በአብዛኛው ወጣት ዘንድ ተስፋፍታ ተለምዳለች መቼም ትርጉሟ የሚገመት ነው የምትለውን አልቀበልም፣ አልሰማህም እንደማለት ነው፡፡ ሌላም ተመሳሳይ አባባል አላት መስሚያዬ ጥጥ ነው/MT/
ሌላው ነባር ቃል ነገር ግን ይዘቱን ቀይሮ በአዲስ መልክ ከተፍ ያለው "ሰምተሃል/ሰምተሻል!" ነው ይህንን ቃል አሁን አሁን የማንሰማበት ቦታ የለም ድሮ ድሮ አንድን ነገር ላለመድገም ስንፈልግ "ጨዋና ራዲዮን አንዴ ነው የሚናገረው" ነበር የሚባለው አሁን አሁን ግን "ሰምተሃል/ሰምተሻል!" ሆኗል፡፡
በነገራችን ላይ ስለዚህ ቃል አመጣጥ የሰማሁትን አፈ-ታሪክ ላውጋችሁ አንድ ሰውዬ ነበር አሉ በአመት ውስጥ መጠየቅ የሚችለው አንድ ጥያቄ  ብቻ ነው ታዲያ አንድ ቀን የረጅም ጊዜ ፍቅረኛውን "የኔ ቆንጆ ለምን አንጋባም?" ሲል ይጠይቃታል ልጅቱ ታዲያ ሰውዬውን እንብዛም አትወደውም ኖሮ "ምን አልከኝ?" ትለዋለች ያልሰማ ለመምሰል፤ ምክንያቱም አመታዊ የጥያቄ ኮታው እንድ ብቻ ነዋ፤ ታዲያ ሰውዬው ምኑ ሞኙ "ሰምተሻል!" ብሎ መለሰላት ይባላል፡፡  
ምንም እንኳን እንደዚህ አይነት ቃላቶች በአብዛኛው በወጣቶች ዘንድ የሚዘወተሩ ቢሆኑም ከላይ እንደጠቀስኩት ቋንቋ ይፈጠራል፣ ይስፋፋል፣ ይለመዳል! ነውና ብሂሉ አሁን አሁን እነዚህን ቃላቶች የሚጠቀሙ በእድሜ የገፉ ሰዎችንም ማስተዋሉ እየተለመደ ነው፡፡ እንደ አብነትም የቅርብ ጓደኛዬን አያት በዋቢነት መጥቀሱ በቂ ነው፤ የጓደኛዬ አያት ከሩቁ ለሚያያቸው ኮስታራና ወግ አጥባቂ ቢመስሉም ለቀረባቸው ግን ተጫዋችነታቸውን ለመገንዘብ ደቂቃ አይፈጅበትም፡፡ ጨዋታ ወዳጅነታቸው የመነጨው በወጣት ልጆቻቸው እንዲሁም የልጅ ልጆቻቸው ታጅበውና ተከበው ውለው ስለሚያመሹ ነው፡፡ ታዲያ ግማሹ ስራ ውሎ፣ ሌላው ትምህርት ውሉ ምሽት ሲገናኙ ሳሎኑ በአንድ እግሩ ነው የሚቆመው፤ ድብልቅልቅ፡፡ አያት ጋቢያቸውን ተከናንበው ሶፋቸው ላይ ተጋድመው ወሬ በያይነቱ መኮምኮም ነው፣ በወጣት ቋንቋ፣ በወጣት አንደበት የሚደሰኮሩትን ሁሉ አፋቸውን ከፍተው ሲኮመኩሙ ማምሸት የዘውትር ልማዳቸው ነው፡፡
ታዲያ አንድ ቀን ይህ ጓደኛዬ ስራ ውሎ መሸትሸት ሲል ወደ ቤት ይገባል፤ እንደ ደንቡም አያቱን እጅ ነስቶ በመኪና ትሸኛለህ የተባለውን ዘመዶቹን መጥተው እንደው ይጠይቃል እንዲህ ሲል "ማማ እንግዶቹ አልመጡም እንዴ?" አያት ሲመልሱ "እረ ወፍ የለም!"
ጓደኛዬ የአያቱ ፍጥነት የተሞላበት ቅፅበታዊ አመላለስ ፈፅሞ ያልጠበቀው በመሆኑ ሶፋ ላይ እየተንከባለለ በግርምት እንደተንከተከተ አጫወተኝ፤ እኔም አያቱን በቅርበት ስለማውቃቸው "እረ ባክህ! ማማ እንዲህ አሉ?" እያልኩኝ አብሬው በሳቅ ፈረስኩ፡፡ "ለመሆኑ ከማን ሰምተው ነው ስለው?" እቺን ሀረግ በተደጋጋሚ የምትጠቀማት የልጅ ልጃቸውን ጠቀሰልኝ፤ እውነትም አልኩ ቋንቋ ይፈጠራል፣ ይስፋፋል፣ ይለመዳል!
ይህን ፅሁፌን ለማዘጋጀት ስሰናዳ እንደ "ሰምተሃል/ሰምተሻል!" ሁሉ ይህቺም ቃል /ወፍ የለም/ መነሻ አፈ-ታሪክ ካላት ብዬ ጠያየኩ አስጠያየኩ ግን አውቃለው የሚል አልተገኘም/ወፍ የለም/፤ ጎሽ! ይኸው አኔም ለመድኩላችሁ፡፡
እኔ እምለው፣ እነዚህ ቃላት የእውነት ተስፋፍተው ቢለመዱስ? መቼም መለመዳቸው አይቀርም፡፡ አንደኛ ጉጉቴ በኢቴቪ/ኢሬቴድ/ አንደበት እነዚህን ቃላቶች ለመስማት ነው፡፡ እንደው ስገምት ጋዜጠኞች ዜና ሲያነቡ እንዲህ ሊሉ ይችላሉ "በየጊዜው እየጨመረ የመጣው የነዳጅ ዋጋ ጭማሬ ያሳሰባቸው የታክሲ ባለንብረቶች ከመንግስት ጋር ባደረጉት ውይይት መንግስት በቀጣይ ጊዜያት የነዳች ዋጋውን ለማረጋጋት ድጎማ ለማድረግ አቅዶ እንደሆነ የጠየቁ ሲሆን መንግስት በበኩሉ "ወፍ የለም!" በማለት በአጭሩ ምላሹን ሰጥቷል አይነት ዜናዎችን መስማታችን አይቀርም ብዬ እገምታለው፡፡                         
ሌላው ጉጉቴ እነዚህን ቃላቶች ፓርላማ ላይ ለመስማት ነው፤ እንኳን እንዲህ አይነት ቃላቶች ታክለውበት ፓርላማችን አሁን አሁን አዝናኝነቱን አልቻልነውም፤ እስኪ አስቡት "የተከበሩ እገሌ… ሰምተዋል!" ምናምን ሲባል፤ ቂቂቂቂ፡፡ እስኪ ለማንኛውም እድሜና ጤናውን ይስጠንና የምንታዘበው ነገር ይሆናል አልሰማንም እንዳትሉ ሰምታችኋል! ሰላም


2 comments: